Translate

Sunday, February 13, 2022

#አባ ቦና ማነው?

<አባ ቦና> ማነው? <አባ ቦና> የሚለውን ቃል በሁለት የተለያዩ ታሪኮች ነው የማውቀው የመጀመሪያው በራያ የሚታወቁት የኩቢ አባቦና ስም ነው። . ዓጤ ዮሀንስ በአዋጅ ራያ ላይ ባካሄዱት ዘመቻ በእርሳቸው ግፊት ወደ ክርስትና የተቀየሩትን የአካባቢውን ገዥወች “ለጉዳይ ፈልጌህ ነው ሰውን ሰብስበህ ጠብቀኝ” እያሉ መልእክት በመላላክ እንጎየ ሜዳ ተሰብስቦ የጠበቃቸውን ወደ 3000 የሚጠጋ የራያ ሰው በአንድ ቀን እንደጨፈጨፉ ታሪክ ያወሳል። በወቅቱ አብረው የተገደሉት የሕዝቡ መሪ "ኩቢ አባቦና" በመባል ይታወቃሉ። አትመነው ትግሬን ቢምል ቢገዘት ክርስትና አንስቶ ኩቢን አረዱት የሚል ስንኝ ከኩቢ አባ ቦና ሞት በኋላ የራያ ሰወች ቋጥረዋል፤ ለትውልድ ተላልፎ ዛሬ ድረስ ይነገራል። . ሌላኛው እና እኔ ስያሜውን ለፌስቡክ ስም ለማድረግ መነሻ ምክንያቱ ደግሞ የደጅ አዝማች ገልሞ ጓንጉል የፈረስ ስም ስለሆነ ነው። ትንሽ ማብራሪያ ለመሰጠት ያክል ዛሬ ድረስ ከመርሳ ከተማ ጋር ተያይዞ ስማቸው ጎልቶ የሚታወቀው ሼኹ አባ ጌትየ ወደ 48 በላይ ልጆች ነበራቸው። . ከእነዚህ መካከል ዝነኛና ታዋቂ የነበሩት እና ክርስትናም ተቀብለው የፈረሳቸው እግር የረገጠበትን ሁሉ እንዲገዙ በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽ ላይ በዳግማዊ ዓጤ እያሱ የተሾሙት አባ ሴሩ ጓንጉል (ጓንጉል አበየ) ናቸው። ጓንጉል በፈረስ ስማቸው አባሴሩ በመባል ነው የሚጠሩት። በፈረስ ስም የመጠራትን ባሕል ለኢትዮጵያ ነገሥታት ያወረሱት የወረሴህና የማመዶች ሥርወ መንግስታት መሳፍንቶች ናቸው ተብሎ ይታመናል። . አባሴሩ ጓንጉል የታወቁ ፈረሰኛ እና መልከ መልካም የሚያምሩ ሰው እንደ ነበሩ በትውፊት ሰምተናል። በተለያየ ጊዜ በርካታ ሚስቶችን አግብተው ከ20 በላይ ልጆችን ወልደዋል። ሚስቶቻቸው ከአምባሰል፣ ከላስታ፣ ከራያ፣ ከየጁ ከቃሊምና ሀብሩ ወዘተ አካባቢወች ነበሩ። አባ ሴሩ ጓንጉል አምባሰልን ጨምሮ ዛሬ ሰሜን ወሎ የሚባለውን አካባቢ እስከ ጨጨሆ በር ድረስ የገዙ ናቸው። . ጓንጉል ከራያ ጉራ ወርቄ ያገቧት ሚስታቸው ወይዘሮ ራጂያ ትባል ነበር፣ ከላስታ ያገቧት ደግሞ ወይዘሮ ገለቡ ፋሪስ ትባል ነበር። ወይዘሮ ገለቡ የላስታው ገዥ የራስ ፋሪስ እህት ነች እያሉ የጻፉ ስወች ቢኖሩም፤ እውነታው ግን የራስ ፋሪስ ልጅ ናት የሚለው ነው። ጓንጉል አባሴሩ ክርስትያን ቢሆኑም የታወቁት የሼኹ አባጌትየ ልጅ በመሆናቸው እስላማዊ ልማዶችና ትውፊቶች በቤታቸው የሚስተዋል ነበር፤ አኗኗራቸውም እንደ ሙስሊም ነበር ይባላል። የላስታው የራስ ፋሪስ ልጅ የሆነችው ባለቤታቸው ወይዘሮ ገለቡ የባሏ ቤተሰቦች የሆኑት ሼኾቹ በቤቷ ዱዐ ሲያደርጉ ጥሩ ሙሪድ ነበረችና በደምብ አድርጋ ስለምትካድማቸው በሼኾቹ ተወዳጅ ነበረች። የጉራ ወርቄዋ ባለቤታቸው ወይዘሮ ራጂያ ደግሞ፤ በሼኾቹ ተመራጭም ተወዳጅም አልነበረችም። ታዲያ ሼኾቹ የጓንጉል ዘመዶች አንድ ቀን በዱዐ መሀል ሀድራው ሲግል . ራጂያ ራጂያ ወለደች አህያ አህያ ገለቡሳ ገለቡሳ ወለደች አምበሳ አምበሳ . በማለት ዋሪዳው በሉ ያላቸውን ብለው ገለቡን በቱፍታቸው አዳረሷት አሉ። መቼም የወረሴሆች ታሪክ ከመዐና ጋር የተያያዘ ነውና የሼሆቹ ዱዐ ሰምሮ ከወ/ሮ ገለቡ የተወለዱት የአባ ሴሩ ልጆች እነ ራስ ቢትወደድ ቀዳማይ ዓሊ ጓንጉል፣ እነ ራስ ቢትወደድ ዓሊጋዝ ጓንጉል፣ የልጅ ልጆቿ እነ ራስ ቢትወደድ ጉግሣ መርሶ የጎንደርን ቤተ መንግስት ተቆጣጥረው፣ ከ65 ዓመት በላይ ማዕከላዊ መንግስትን በበላይነት እየመሩ፣ የፈለጉትን እያነገሡ ያልፈለጉትን እያወረዱ አድራጊ ፈጣሪ ሆነው የዚያኔዋን ኢትዮጵያ ገዙ። ከወ/ሮ ራጂያ የተወለዱት እነ ደጃዝማች ወሌ ጓንጉል፣ እነ ደጃዝማች ገልሞ ጓንጉል ገዥነታቸው በአካባቢያቸው የተወሰነ በመሆኑ በየጁ፣ ራያ እና ላስታ ብቻ አልፈው አልገዙም። . በተለይ የአባ ሴሩ ጓንጉል ወራሽ ይሆናል የተባለው የደጃዝማች ወሌ የአምበሳ ደቦል ካላመጣችሁ እያለ ሕዝብ የሚያስቸግር ተንኮለኛ ነበረና መጨረሻው የማያምር ነበር። የደጃማች ወሌ ወንድም የወይዘሮ ራጂያ ልጅ የደጃዝማች ገልሞ ጓንጉል የፈረስ ስሙ አባቦና ይባላል። ደጃዝማች ገልሞ ጓንጉል በተለምዶ በዜና መዋዕልም ጭምር <አባቦና ገልሞ> እየተባለ ነበር የሚጠራው። ቦና በዚህ አገባብ ትርጉሙ <ኩራት> ማለት ነው።

No comments:

Post a Comment

mootittii saba'a Queen of sheba

"Mootittii Saba'a""Queen sheba" ----------------------------------------------------------------- ★Miky Sultan Bar...