Translate

Wednesday, February 2, 2022

#ግሼ አባይ ፣ ምነኛ ነው?

ግሼ አባይ፣ ምንኛ ነው? ግሴ አባይ ማለት በቅማንትኛ ግልገል አባይ ወይም ድንክ አባይ ማለት ነው። ደብተራው ግን ሊያጥፋፋ ይዳክራል። እውነት የትኛውንም ያክል በገድል ልትሸፍነው ብትሞክር አይሸፈንም። ~~~~ ግሼ ዓባይ፡ ምንኛ ነው? ~~~~~~~~~~~~ መቼም የእኛ አገር ውስጥ ብዙ ነገሮች ትክክለኛ ማንነታቸውና የስማቸው ትርጉም በውል አይታወቅም። ምክንያቱም ሀገሪቱ ላለፉት አያሌ ምእት ዓመታት የሆነ የታሪክ ነቀዝ አፍርታ ትክክለኛውን የታሪካችን ፍሬ በልቶ እንክርዳዱንና ግርዱም ጥሎልን በመሄዱ ነው። ከሰዎች የስም ስያሜዎች እንኳ ብንነሳ አያሌ ትርጉም የለሽ ስሞች ሞልተዋል። ለምሳሌ ጋሼ፡ ፈንቴ፡ ፈንቲ፡ ወሰንጌ፡ ጀጃው፡ ገልሞ፡ ኮልቫ፡ ጉርባ፡ አስሜ፡ ሰጤ፡ ወዘተ የሚሉትን ስሞች ብንመለከታቸው በአማርኛ፡ በትግርኛ፡ በግዕዝ ወይም በሌላ ማንኛውም ቋንቋ ትርጉም የላቸውም። ይሄ ለምን ሆነ? የሚል ጥያቄ ስናነሳ መልሳችን የሚሆነው "የታሪክ ቀበኞች የሆነን ታሪካዊ ሕዝብ ደዝባ ለማጥፋት ስለሠሩ ነው" የሚል ይሆናል። ~~~ ይሄ ትርጉም አልባነት በሰዎች ስታሜዎች ብቻ ተወስኖ የሚቀር ሳይሆን በተለያዩ መልክዓ ምድራዊ ስያሜዎችም ላይ ጎልቶ ይታያል። ለምሳሌ ከመካከለኛው ኢትዮጵያ እስከ ግብፅ ድንበር ያሉ የተለያዩ መልክዓ ምድራዊ ሥያሜዎችን ስንመለከት ከላይ በጠቀስኳቸው ቋንቋዎች ምንም ዓይነት ትርጉም የላቸውም። ሸዋና ሸዋ ውስጥ ያሉ ቦታዎች፡ ጎጃምና ጎጃም ውስጥ ያሉ ቦታዎች፡ ጎንደርና ጎንደር ውስጥ ያሉ ቦታዎች (ካና ሰጌ)ን ጨምሮ፡ ወሎና ወሎ ውስጥ ያሉ ቦታዎች፡ ትግራይና ትግራይ ውስጥ ያሉ ቦታዎች፡ ኤርትራና ኤርትራ ውስጥ ያሉ ቦታዎች፡ ወዘተ አብዛኛዎቹ ብዙዎቻችን በምናውቃቸው ቋንቋዎች ትርጉም የላቸውም። ለምን? እውን ትርጉም የሌላቸው ናቸውን? ~~~ በእርግጥ ትርጉም አላቸው። ትርጉማቸውም አንዳንዶች ራሳቸውን አጥፍተው ሌላውን ለማጥፋት ታሪክ የሚደልዙና የሚደርቱ የታሪክ ድሪቶ ጸሓፍት እንደሚሉት በአረብኛና በኢብራይስጥ ሳይሆን በጥንታዊው የሰው ልጆች አባት ቋንቋ በቅማንትኛ( ኬሜንት) ኩሽ የሚፈታ ነው። ይሄን እውነታ ስጽፍ ብዙ የውሸት ታሪክ ተስፈኞች የተለመደ የስድብና የፉከራ መርዛማ ምላሳቸውን መቀሰራቸው የተለመደ ነው። በእርግጥ እነሱ ስለተሳደቡና ስለሚዝቱ ፈርቼ እውነትን ከመናገር አልገታም። እውነት ያሸንፋልና ለኢትዮጵያ የኋላቀርነትና የድንቁርና መሠረት የሆነውን የታሪክ ድሪቶ ማፈራረስና እውነታን የማውጣት ኅሊናዊ ኃላፊነት ስላለብኝ በህይወት እስካለሁ ድረስ እውነታውን ከማውጣት የሚያግደኝ ፉከራም ሽለላም፡ መተትም ድግምትም አይኖርም። እውነት ከኮልኮሌያም ጠንቋዮችና ደብተራዎች በላይ ናትና አልፈራም። ~~~ በርእሰ ጉዳዩ ላይ ወደ አነሳሁት "ግሼ ዓባይ" ልመለስ። ዓባይ የሚለው ቃል በኋላ የተሰየመ ከግዕዙ "ዓበየ" ተለቀ ከሚለው ግስ ወጥቶ የተሰጠ ስያሜ እንደሆነ ደብተራው ጽፏል። በመሆኑም ዓባይ ትልቅ እንደማለት ነው። ትግርኛውም "ዓባይ ገረብ፡ ዓባይ ገለመሌ" ሲል ይሰማል። የዓባት ጥንታዊ ስሙ ግን "ጊዮን" ነው። ለዚህ ማስረጃ በታላቁ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ኦሪት ዘፍጥረት ምእራፍ 2 ቁጥር 13ን ተመልከትልቹ። እንዲህ ይላል። "ወስሙ ለካልእ ፈለገ ጊዮን ውእቱ ዘየዐውድ ኩሎ ምድረ ኢትዮጵያ" ይላል። ትርጉሙም "የሁለተኛው ስሙ የጊዮን ወንዝ ይባላል፡ እርሱም የኢትዮን ምድር የሚከበው ነው" ማለት ነው። ~~~ ለመሆኑ "ጊዮን" ማለት ምን ማለት ነው? "ጊዮን" ከ"ሌጊዮን" ጋር የሚያያዝ ትርጉም አለው። "ሌጊዮን" ማለት የአጋንንት መንጋ ማለት እንደሆነ ቅዱስ ወንጌላችን ይነግረናል። ነገር ግን በምን ቋንቋ መሆኑን አናውቅም። ያም ይሁን ይህ ግን "ሌግዮን ማለት በቅማንትኛ "መቶ አጋንንት" ማለት ነው። (ሊጝ + ጊዮን = መቶ + አጋንንት)። ይህ የሚያሳየን "ሌጊዮን" ማለት የ100 ጋኔኖች መንጋ በአንድ ብርጌድ ማለት መሆኑን ነው። ~~~ ይሄ "ሌጊዮን" የሚባለው ርኩር መንፈስ በጣናው ዘጌ ለብዙ ዘመናት ሰዎችን ነጭ በሬ እና ጥቁር ዶሮ እያሳረደ ሲመለክ የኖረ የዲያብሎስ መንፈስ ነው። ዛሬም ድረስ ጣና ሰው ሲበላ የአካባቢው ሰው የዋጠውን ሰው አስከሬን ከጣና የሚረከበው ጥቁር ዶሮ አርዶ ወደ ሐይቁ በመወርወር ነው። ይሄን በተመለከተ ከዚህ በፊት "ካና ሰጌ" በሚል ርእስ የፃፍኩትን ጽሑፍ ማንበብ ጥሩ ነው። የቀደሙ ቅማንቶች ለምን ይህን ወንዝ "ጊዮን" ወይም "አጋንንት አሉት?" ብለን ስናስብ ብዙ ታሪካዊና ስነልሳናዊ ምርምሮችን ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን መረዳት ግድ ይላል። እንዲያው ኅሊናየ የሚጠረጥረውን ለመናገር ያክል ግን ከላይ ካነሳሁት በአድ አምልኮት ጋር መያያዙን እምብዛም አልጠራጠርም። ዙሮ ዙሮ ግን ትርጉሙ ምንም ይሁን ምን "ጊዮን" አሁን "ዓባይ" ብለን የምንጠራው የአንድ ትልቅና ረዥም ወንዝ ሥያሜ ነው። ~~~ ዓባይ ከሚለው ወንዝ ላይ በመጨመር የምንጠቀምበው "ግሼ" የሚለው ስም አጎላማሽ ወይም አኮሳሽ ቅጽል ምን ማለት እንደሆነ ድግሞ ከዚህ ቀጥለን እንመልከት። "ግሼ" የሚለው ቃል ብዙዎቻችን ደጋግመን እንሰማዋለም። "ግሼ ዓባይ፡ ግሼን ደብረ ከርቤ፣ ወዘተ" እየተባለ ሲጠራ እንሰማለን። በነገራችን ላይ "ግሼን" ማለት የ"ግሼ" ብዙ ቁጥሩ መሆኑን ማሳሰብ እፈልጋለሁ። ~~~ በቅማንትኛ "ግሼ/ግሴ" ማለት "አጭር፡ ድንክ፡ በአካል ትንሽ የሆነ" ማለት ነው። ቅማንቶች "ድንክ ሰው" ሲያዩ "ግሴ ይር" ይሉታል። "ድንክ አልጋ" ለማለትም ደግሞ "ግሴ አርግ" ይላሉ። ቃሉ የስም ገላጭ ወይም ቅጽል ነው። ከስም ጋር እየገባ ስምን ይገልፃል። ለዚህም ነው "ግሼ ዓባይ" የሚባለው። የሆነን የዓባይ ክፍል ከሌላው የዓባይ ግፍል ለመለየት ይረዳ ዘንድ አባቶቻችን ዓባይ በሚለው ስም ላይ "ግሴ" የሚል ቅጽል ቀጽለውበታል። ~~~ "ግሴ ዓባይ" ወይም "ግሼ ዓባይ" የሚለውን ቃል በቃል ስንተረጉመው "ድንክ ዓባይ፡ ትንሹ አባይ፡ አጭሩ አባይ" ማለት ነው። ይሄ የዓባይ ስያሜ የሚያገለግለው ከዓባይ ምንጭ ከሰከላ (ሰቀላ) እስከ ጣና ዘጌ (ካና ሰጌ) ላለው የዓባይ ወንዝ ክፍል ብቻ ነው። ይሄን የዓባይ ክፍል የአካባቢው ሰው በተለምዶ "ግልገል ዓባይ" እያለ ይጠራዋል። ቢኮሎ (መሬት ሰብሮ) ዓባይ የምትባለው ትንሽዬ ከተማ ደርሳችሁ " ይህ ወንዝ ማን ይባላል?" ብላችሁ ማንኛውንም ሰው ብትጠይቁ ያለምንም ጥርጥር "ግልገል ዓባይ ይባላል!" ይሏችኋል። ይሄ ትክክለኛው የ"ግሴ/ሼ ዓባይ" ትርጉም ነው። "ግልገል ዓባይ" ማለትና "ትንሹ ዓባይ" ወይም "ድንኩ ዓባይ" ማለት አንድ ናቸው። ግልገል ከእናቱ ወይም ከአባቱ አንፃር ሲታይ ድንክ ወይም በጣም ትንሽ ነው። ስለዚህ ይሄ የአማርኛው "ግልገል ዓባይ" እና የቅማንትኛው "ግሴ ዓባይ" ምንም ዓይነት የትርጉም ልዩነት የላቸውም። እናም "ግሴ/ግሼ ዓባይ" የሚለው ስያሜ ለ"ግልገል ዓባይ" የተሰጠ ስያሜ መሆኑን ልብ ይሏል። ~~~ የ"ግሼ/ግሴ ዓባይ" ትክክለኛው ትርጉም ይሄ ሆኖ እያላ የታሪክ ላጲስ ደብተራዎች ያልሆነ ድሪቶ ታሪክ ፈጥረው ሲንደፋደፉና ሲያደነቁሩን ይስተዋላሉ። እነርሱ እንዲህ ይላሉ፡ "አንድ የበቁ መነኩሴ ዳዊታቸውን ሰከላ ለሚገኘው የዓባይ ምንጭ አደራ ሰጥተውት ወደ ሌላ አገር ሄዱ። ከብዙ ዓመታት በኋላ ወደ ሰከላ ተመልሰው የዓባይን ምንጭ 'በአደራ የሰጠሁሽን ዳዊቴን ግሺ'! ቢሏት ምንጯ ዳዊታቸውን አውጥታ ሰጠቻቸው። ከዚህም የተነሳ ቦታው 'ግሼ ዓባይ' ተባለ" ይሉናል። ሲጀመር ይሄ አባባል በብዙ መንገዶች ስህተት ነው። 4ቱን ስህተቶች አንስቼ ላብራራ። ~~~ አንደኛው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ታሪክ ውስጥ የበቃ መነኩሴ ዳዊት አንጠልትሎ አይሄድም። የበቃ መነኩሴ ማለት ሁሉም የተገለጠለት ሁሉን ጸሎቶች በልቡ የተጻፉለት ቅዱስ ሰው ማለት ነው። ስለዚህ የዚህ ትፈታሪክ ዋና የክርክር ነጥብ ተቀባይነት የሌለው የክርክር መነሻን የያዘ በመሆኑ ታሪኩ የተፈለሰፈ ኢ-አመክንዮአዊ ነው። ~~~ ሁለተኛው ምንጯ አማርኛውን አጣማ ነው የተረዳችው። ምክንያቱም መነኩሴው "ግሽልኝ!" እንጂ "ትፊልኝ ወይም አስመልሽልኝ ወይንም አቀርሽልኝ!" አላላትም። እሱ ያላት "ግሽልኝ!" ነው። "ማግሳት" ማለት የሆነ ምግብ በልተን ወይም መጠጥ ጠጥተን ስናበቃ ከምግቡ ወይም ከመጠጡ ጋር ወደ ጨጓራችን ውስጥ የገባው አየር ተመልሶ በአፋችን ሲወጣ የሚፈጠር የድምጽ ክስተት ነው። የበላነውን ካስታወክነው ወይም ካቀረሸነው ግን ወደ ጨጓራችን ያስገባነውን ምግብ ወይም መጠጥ መልሰን ባፋችን ማውጣታችን የሚያሳይ ነው። እናም መነኩሴው ማለት የነበረበት "ግሺ" ሳይሆን "አስታውኪልኝ!" ወይም "አቀርሽልኝ!" ነበር። እርሱ በተበላሸ አማርኛ "ዳዊቴን ግሺ" ሲላት ምንጯ ከዳዊቱ ጋር ወደ ሆዷ የገባውን አየር ብቻ ቡልቅ ማድረግ ነበረባት። ነገር ግን ምንጯም እንደ አለቆቿ ቀጣፊ ነች ማለት ነው። "ግሽልኝ!" ስትባል የምታስታውክ ወይም የምታቀረሽ "ሳይጠሯት አቤት ሳይልኳት ወዴት!" የምትል ቅላጥቤ የሆነች ምንጭ መሆኗ አያስገርማችሁም!? መነኩሴውም ቢሆኑ "የሰጠሁሽ ዳዊት መልሽ!" ብሎ በቀጥታ ከማዘዝ ይልቅ ለምን "ግሽልኝ፣ ፍሽልኝ!" ማለት አስፈለጋቸው? ይሄ ሁሉ ዝባዝንኬ የሚወራው የፈጠራ ድሪቶ ታሪክ እንጂ እውነት አለመሆኑን በዚህ እንረዳለን። ~~~ ሦስተኛው "ግሼ" የሚለው ስያሜ የሚገኘው በዚህ በሰከላው የዓባይ ምንጭ ላይ ብቻ ሳይሆን በሌላው የሃገሪቱ ክፍሎች ይገኛል። ለምሳሌ የግሼን ደብረ ከርቤ ማርያምን ስያመ መመልከት እንችላለን። በነገራችን ላይ ቀደም ሲል እንደጠቆምኩት "ግሴ/ግሼ" (ድንክ/በጣም አጭር) ብለን "ግሴን/ግሼን" ስንል "ድንኮች" ማለታችን መሆኑን አይተናል። ለማንኛውም ግን ደብተራው ለምን "ግሼን ደብረ ከርቤ" እንደተባለ የደረተው ታሪክ ይኑር አይኑር አላነበብኩም። ሳስበው ግን ሳይደርቱ አይቀሩም። ሳገኘው አጋራችኋለሁ። በዚህ በሁለተኛው ምክንያት አንፃርም ስናየው የግሼ ዓባይ ተረት ተረት ከድሪቶነት ታሪክ አያልፍም። ~~~ አራተኛው ደብተራው ይሄን የፈጠራ ድሪቶ ታሪክ ሲደርት ምንጯ ከመነኩሴውና ከእርሷ ግንኙነት በፊት ማን ተብላ ትጠራ እንደነበር የነገረም ምንም ፍንጭ የለም። ልክ "አፄፋሲለደስ አሁን ፋሲል ግንብ የተሠራበት ቦታ ሲደርስ የበቁ መነኮሳትን በዛው ሲፀልዩ አገኝቶ የሚሆነውን ነገሩት" ብለው እንደደሰኮሩት ድሪቶ ታሪክ ማለት ነው። ምክንያቱም አሁን ፋሲል ግን የተሰራበት ቦታ "ምዝገኒ" በመባል የሚታወቅ የቅማንት የህገልኑና የጸሎትና የመስዋእት ማቅረቢያ ድግና የነበረ እንጂ የክርስቲያን መነኮሳት መኖሪያ ገዳም አለነበረው። "የበቁ የቅማንት ባቲዋዎችን አግኝቶ እንዲህ አሉት" ላለማለት ዝም ብለው ወደ ራሳቸው መደረታቸው ልማድ ነውና እንዲህ ሲያደርጉ ኖሩ። የግሼውም ተረት ተረት "ግሴ/ግሼ" ቅማንትኛ ነው ላለማለት ያለፈውን እውነተኛ ስያሜ አይናገሩም። ዓላማቸውም የቀደመውን እውነተኛ ታሪክ ማጥፋት ስለሆነ ፈጠራቸውን እንጂ የቀደመውን አይነግሩንም። ለመንገርም ወኔና ሞራል የላቸውም። ~~~ ይሄ የግሼው ተረት ተረት እነዚህ ደብተራ ዘኮልኮሌና ዘዝባዝንኬዎች በምን ያክል ደረጃ የኢትዮጵያን ታሪክ ገድለው በትልቅ የድሪቶ ታሪካዊ ጉድጓድ እንደቀበሩት የሚያሳይ ጥሩ አብነት ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ እውነተኛ ሕዝቦችና ታሪኮቻቸው እንዲህ ተደርጎ በመቀበሩ ምክንያት በድንቁርና አዙሪት ውስጥ ወድቀን ተቸግረናል። ታሪካዊ፡ ባህላዊ፡ ማህበራዊ፡ ፖለቲካዊና ምጣኔ ሃብታዊ ሕይወታችን ሁሉ እንደተጎለጎለ ልቅ ዐይኑ ጠፍቶብን እንደራገማለን። በዚች ሃገር እርስ በርስ መገዳደል የተጀመረው በእነዚህ የታሪክ ድሪቶ ጎታቾች መፈጠር ምክንያት ለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም። እነዚህ ናቸው በህዝቦች መካከል ክፍፍልን የፈጠሩት። ያልሆኑትን ሰልሙነው ቅጥቅጥ ሰሎሞናዊያን ሆነው ሌላውን በግደል ጀመሩ። መድሃኒቱ አሁኑኑ ነቅተን ወደ ትክክለኛ ታሪካችን መመለስ ነው። ደብተራው በራሱብቁመቱና ወርዱ ልክ ሰፍቶ ያለበሰንን የታሪክ ድሪቶ አውልቀን መጣል ይኖርብናል። ከደብተራ ታሪክ ካልወጣን መፍትሔ የለውም። Website:-https://mikysultan.blogspot.com/ Youtube:-https://youtu.be/CdY1umekwpU Telegram:- t.me/Oromo_ geography

No comments:

Post a Comment

mootittii saba'a Queen of sheba

"Mootittii Saba'a""Queen sheba" ----------------------------------------------------------------- ★Miky Sultan Bar...